በአምቦ ዩኒቨርስቲ ስልጠናቸውን ሲከታተሉ የቆዩ የ11ኛ ዙር የሰላም በጎ ፈቃደኞች ተመረቁ
በአምቦ ዩኒቨርስቲ ስልጠናቸውን ሲከታተሉ የቆዩ የ11ኛ ዙር የሰላም በጎ ፈቃደኞች ተመረቁ
ኅዳር 29 ቀን 2017 ዓ.ም የሰላም ሚኒስቴር ከአምቦ ዩኒቨርስቲ ጋር በመተባበር በ11ኛው ዙር መርሐ-ግብር ያሰለጠናቸውን የሰላም በጎ ፈቃደኛ ወጣቶችን በአምቦ ዩኒቨርስቲ አስመርቋል።
የምረቃ ስነ ስርዓቱ በሐይማኖት አባቶች ምርቃት ተጀምሯል።
በምረቃ መርሐ ግብሩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፋት በሰላም ሚኒስቴር የሚኒስትሩ አማካሪ አምባሳደር እሸቱ ደሴ "በጎነት ለአብሮነት በሚል መሪ ሐሳብ በሰላም ሚኒስቴር የተጀመረው የሰላም የወጣቶች በጎ ፈቃድ የማኅበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም ዓላማ የወጣቱን አመለካከት፣ ክህሎትና ሞራል በመገንባት እንዲሁም አንዱ የሌላውን ባህልና እሴት እንዲያውቅ በማድረግ ፤ በማንነቶች ላይ መሠረት አድርጎ ያለውን አለመግባባት በማስወገድ የሀገራችንን ዘላቂ ሰላምና ብሔራዊ መግባባት ማረጋገጥ መሆኑን ተናግረዋል።
ይህ ፕሮግራም ወጣቶች ማህበረሰባዊ እሴቶችን እና የሞራል አቅም እንዲያጎለብቱ በመደገፍ በተለይም ብዝሃነት ባለበት እንደ ኢትዮጵያ ያለ ሀገር ውስጥ እርስ በርስ መደማመጥና መረዳዳትን ለማምጣት ሚናው የጎላ ነው ያሉ ሲሆን አንዱ የሌላውን እሴቶችንና ባህል እንዲያውቅና እንዲያከብር ግንዛቤን ያስጨብጣል ብለዋል።
የሰላም ሚኒስቴር አወንታዊ ሰላም ከሚገነባባቸው መንገዶች መካከል አንዱ የብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም መሆኑን የገለፁት አምባሳደሩ በዚህ ፕሮግራም የተሳተፉ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች በመላው ሀገሪቱ የሰላም አምባሳደሮች ሆነዋል፣ ህዝብ የማቀራረብ ስራ ሰርተዋል፣ማህበራዊና ባህላዊ እሴቶቻችን እንዲዳብሩ አድርገዋል፣ ብዝሃነትን እንደ በጎ እድል የመቆጠር ሃሳብ አድጓል፣ በጎ የመስራት ሃሳብ ጎልብቷል፤ በአጠቃላይ ኢትዮጵያዊነት የሚለው ስሜት ከፍ እንዲል የተለያዩ ተግባራትን አከናውነዋል ብለዋል።
የሰላም ሚኒስቴር የብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ገመቺስ ኢቲቻ ለተመራቂ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ባስተላለፉት መልዕክት በጎ ፈቃድ መስራት ዕድለኝነት ነው ያሉ ሲሆን ይህ ፕሮግራም ኢትዮጵያን የምታዩበት ፣ በተለያዩ የሀገራችን ክፍል የሚገኙ ባህሎችንና ዕሴቶችን የምታውቁበት ፕሮግራም ነው ብለዋል።
የአምቦ ዩኒቨርስቲ ፕሬዝዳንት ተወካይ ፕሮፌሰር ብዙነሽ ሚዲቅሳ በበኩላቸው ኢትዮጵያ የሰላም፣የብዝሃነት፣የአንድነት እና የእኩልነት ሀገር ሆና እንድትቀጠል የበጎ ፈቃድ ስራ በእጁጉ ያስፈልጋል ያሉ ሲሆን ዛሬ የተመረቃችሁ የሰላም በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ለዩኒቨርስቲያችን ውበትና ኩራት ነበራችሁ፤ በሄዳቹሁበት ሁሉ የሰላም አምባሳደር ሁናችሁ እንድታገለግሉ ጥሪ አስተላልፋለሁ ብለዋል።
የአቦ ዩኒቨርስቲ ምክትል ፕሬዝዳንት ሰለሞን አለሙ (ዶ/ር) ዛሬ የተመረቃችሁ የብሔራዊ የበጎፈቃድ ማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም ወጣት ሰልጣኞች በምትሄዱበት ሁሉ በራሳችሁ ተነሳሽነት በማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ ጉዳዮች ላይ በንቃት በመሳተፍ ለሐገራችንን ሁለንተናዊ እንቅስቃሴ የበኩላችሁን እንድትወጡ አደራ ማለት እፈልጋለሁ ብለዋል፡፡
በ11ኛ ዙር የብሔራዊ የበጎ ፈቃድ የማህበረሰብ አገልግሎት ፕሮግራም ሲሰለጥኑ የቆዩ በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ከስልጣናቸው ጎን ለጎን የተለያዩ የማህበረሰብ አገልግሎት ሲሰጡ የቆዩ ሲሆን የአቅመ ደካማ ቤቶችን ማደሳቸውንና የደረሰ ሰብል መሰብሰባቸው ተገልጿል