ሀገራዊ የሰላምና ፀጥታ ትብብር ሪቂቅ ቻርተር ላይ ውይይት ተካሄደ
ሀገራዊ የሰላምና ፀጥታ ትብብር ሪቂቅ ቻርተር ላይ ውይይት ተካሄደ
ኅዳር 25 ቀን 2017 ዓ.ም በሰላም ሚኒስቴር እና የክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮዎች የጋራ የሰላምና ጸጥታ የትብብር ቻርተር ግብዓት ማሰባሰቢያ መድረክ ተካሂዷል፡፡
በመድረኩ ላይ ተገኝተው መልዕክት ያስተላለፉት የሰላም ሚኒስቴር የፌዴራሊዝምና መንግስታት ግንኙነት መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ወንድማገኝ ኃይሌ የሀገራችን ዘላቂ ሰላም እንዲረጋገጥ እና የተረጋጋች ሀገር እንድትኖረን ቅንጅታዊ አሰራር እና ትብብር እንደሚያስፈልግ ገልፀው ለዚህ ነው ሀገራዊ የሰላምና የፀጥታ ትብብር ረቂቅ ቻርተር ማዘጋጀት ያስፈለገው ብለዋል፡፡
ይህ ሀገራዊ የሰላምና የፀጥታ ትብብር ሪቂቅ ቻርተር በኢትዮጵያ ፌዴራላዊ ዴሞክራሲያዊ ሪፐብሊክ የመንግስታት ግንኙነት ሥርዓት ለመወሰን በወጣው አዋጅ ስር የሚገኝ ሲሆን ዓላማው ዘላቂ ሰላምን በማስፍን፣ ፈጣን ልማትን ለማረጋገጥ፣ ዋስትና ያለው ዴሞክራሲን ለመገንባት እና መልካም አስተዳደርን ለማስፈን ምቹ ሁኔታን በመፍጠር የሀገሪቱን ህዝቦች የጋራ ተጠቃሚነትን በማረጋገጥ እንዲሁም ትስስራቸውን በማጎልበት ስርዓቱን ማጠናከር መሆኑን ተናግረዋል፡፡
“በሰላም ሚኒስቴር እና የክልል ሰላምና ፀጥታ ቢሮዎች የጋራ የሰላምና ጸጥታ የትብብር ቻርተር” ሰነድ በሰላም ሚኒስቴር የመንግስታት ግንኙነት ዴስክ ኃላፊ አቶ ግርማ ቸሩ በኩል ቀርቦ የቡድን ውይይት ተደርጎበታል፡፡
የውይይቱ ተሳታፊዎች ለቻርተሩ ግብዓት የሚሆኑ ሃሳቦችን አንስተዋል፡፡
በመድረኩ ላይ ተገኝተው ለተነሱት ሃሳቦች ማጠቃለያ የሰጡት የሰላም ሚኒስቴር የፌዴራሊዝምና ግጭት አስተዳደር ዘርፍ ሚኒስትር ዴዔታ ክቡር አቶ ቸሩጌታ ገነነ በመድረኩ ላይ ጠቃሚ ሃሳቦች እንደተነሱ ገልፀዋል፡፡
ለውጥ ወደ ተግባር እንዲገባ እና ውጤታማ እንዲሆን ተቋማዊ መሆን አለበት ያሉት ሚኒስትር ዴዔታው ይህ ቻርተር ያሉንን ግንኙነቶች ተቋማዊ በማድረግ እያጋጠሙን ያሉትን ችግሮች በዘላቂነት ለመፍታት ትልቅ አቅም ይፈጥራል ብለዋል፡፡
ክቡር አቶ ቸሩጌታ አክለውም ለሰላም ዕጦት መንስዔ ከሚሆኑ ጉዳዮች አንዱ ተናቦ አለመስራት ነው ያሉ ሲሆን ይህ ቻርተር ተናቦ እና ተቀናጅቶ ለመስራት በር ይከፍታል ብለዋል፡፡