የ11ኛ ዙር በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ስልጠና መርሐ-ግብር መክፈቻ ሥነ-ስርዓት በአምቦ ዪኒቨርሲቲ ተከናውኗል፡፡
የ11ኛ ዙር በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ስልጠና መርሐ-ግብር መክፈቻ ሥነ-ስርዓት በአምቦ ዪኒቨርሲቲ ተከናውኗል፡፡
ኢትዮጵያዊ እሴቶችን ለወጣቱ ትውልድ ማስተላለፍ ሀገራዊ አንድነትና ብሔራዊ መግባባትን ለማስፈን የጎላ ሚና እንዳለው ተገለጸ።
ኅዳር 12 ቀን 2017 ዓ.ም (የሰላም ሚኒስቴር ) የሰላም ሚኒስቴር ብሔራዊ የበጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት 11ኛ ዙር በጎ ፈቃደኛ ወጣቶች ስልጠና መርሐ-ግብር መክፈቻ ሥነስርዓት በአምቦ ዪኒቨርሲቲ ተከናውኗል፡፡
በሰላም ሚኒስቴር የሚኒስትሩ ልዩ አማካሪ ክቡር አቶ ካይዳኪ ገዛኸኝ በስልጠና መክፈቻ ሥነ ስርዓት ላይ ባደረጉት ንግግር "የበጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት ሥራ ላይ መሳተፍ የህሊናና የመንፈስ እርካታ የሚሰጥ እና በሀገራዊ መግባባት ሥራ ውስጥ የራሳችሁን አዎንታዊ አሻራ በማሳረፍ ሀገር እና ወገን ታላቅ ውለታ የምትሠሩበት ነው" ብለዋል።
መርሐ ግብሩ የወጣቱን አመለካከት፣ ክህሎትና ሞራል በመገንባት እንዲሁም አንዱ የሌላውን ባህልና እሴት እንዲገነዘብ በማድረግ ብሔራዊ መግባባትን የሚፈጥር እና ለሀገራችን ሰላምና አንድነት መጠናከር የጎላ ሚና ያለው መሆኑንም ክቡር አቶ ካይዳኪ አስገንዝበዋል።
የአምቦ ዩኒቨርሲቲ ፕሬዚዳንት ባይሳ ለታ (ዶ/ር) ባደረጉት የእንኳን ደህና መጣችሁ ንግግር " ኢትዮጵያ አሁን ባለችበት ሁኔታ ሚታየውን አለመግባባቶች ለመስበር የዜጎቿን ሁለንተናዊ አገልግሎት ትፈልጋለች። እንደ አንድ ሀገር ዜጋ ርስ በራሳችን በመተዋወቅ እና በመረዳዳት ሀገራችን ሰላሟ እንዲጠበቅ የጋራ ርብርብ በሚያስፈልጋት ጊዜ ላይ ነን። ለዚህ ታላቅ ዓላማ በመነሳታችሁም ለሀገር ብዙ ያበረከታችሁ በመሆናችሁ እንኳን ደስ ያላችሁ" በማለት መልእክት አስተላልፈዋል።
የብሔራዊ በጎ ፈቃድ ማኅበረሰብ አገልግሎት መሪ ሥራ አስፈፃሚ አቶ ገመቺሳ ኢትቻ ስለ ስልጠናው በሰጡት ማብራሪያ "ከመላው ሀገራችን ተሰባስባችሁ የሰላም አምባሳደር እና የበጎነት ተምሳሌት የሆናችሁ ወጣቶች በስልጠና ቆይታችሁ ኢትዮጵያዊ ባህሎቻችንን፣ ቋንቋዎችን እና እሴቶቻችንን በመጋራት ሀገራዊ ሕብር የምታጠናክሩበት፤ በስልጠናው የምታገኙትን ዕውቀትና ክህሎት ተጠቅማችሁ ሀገርን እና ወገንን ለማገልገል የምትዘጋጁበት ነው" ፤ ሲሉ መልዕክት አስተላልፈዋል።
ወጣቶች በሀገር ግንባታ ስለሚኖራቸው ሚና ግንዛቤ በመጨበጥ ገንቢ በሆነ መንገድ እንዲሳተፉ እና ማህኅበራዊ እሴቶችን እንዲያዳብሩ ማስቻል፣ ለሀገራችን የዘላቂ ሰላም ግንባታ ድርሻው የላቀ ስለሆነ በክሕሎት፣ በሥነ ምግባር፣ በሥራ ፈጠራ አቅማቸውን የሚያዳብር ስልጠና እንደሚሰጣቸው ተገልጿል።