የሰላም ሚኒስቴር አመራሮችና ሠራተኞች በብሔራዊ ጥቅም እና ጂኦስትራቴጂ ጉዳዮች ውይይት አደረጉ
የሰላም ሚኒስቴር አመራሮችና ሠራተኞች በብሔራዊ ጥቅም እና ጂኦስትራቴጂ ጉዳዮች ውይይት አደረጉ
ጥቅምት 7/2018 ዓ.ም (የሰላም ሚኒስቴር) ፣ የሰላም ሚኒስቴር አመራሮችና ሠራተኞች "ብሔራዊ ጥቅም እና የጂኦስትራቴጂ ቁመና" በሚል ርዕስ ለመንግሥት ሠራተኞች በተዘጋጀ ሰነድ ላይ ውይይት አድርገዋል።
ውይይቱን በንግግር የከፈቱት የሰላም ሚኒስቴር የሰላም ግንባታና ብሔራዊ መግባባት ዘርፍ ሚኒስትር ዲኤታ ክቡር ከይረዲን ተዘራ (ዶ/ር)፡ የኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና የጂኦስትራቴጂ ጉዳይ የፖለቲካ ጉዳይ ብቻ ሳይሆን የእያንዳንዱ ዜጋ ጉዳይ መሆኑን አሳስበው፣ ሰነዱ የተዘጋጀበትም ዓላማ አሁን ካለንበት ችግር ወጥተን ለትውልድ የሚሆን ሥራ መሥራት አስፈላጊ መሆኑን አስገንዝበው ይህም የመንግሥት ጉዳይ ብቻ ሳይሆን ሁሉም ሊረዳው የሚያስፈልግ ጉዳይ መሆኑን ገልፀዋል።
ክቡር ሚኒስትር ዲኤታው አክለውም ስልጠናው ኢትዮጵያን በልኳ ተገንዝበን ለሌሎች ለማስገንዘብ እና እንደ ሰላም ሚኒስቴር ተልዕዃችንን ለማሳካት ቀጥተኛ ግብአት ልንሆን እንደምንችል ተናግረዋል። ያለንን ፀጋ፣ ዕድልና እምቅ አቅሞቻችንን በተገቢሁ ሁኔታ ተጠቅመን ብሔራዊ ጥቅማችንን ለማስጠበቅ እና ሀገራችንን ለማሳደግ በጋራ መቆም እንደሚያስፈልግም አሳስበዋል፡፡
በኢትዮጵያ ብሔራዊ ጥቅምና የጂኦስትራቴጂያዊ አቋም ዙሪያ የተዘጋጀውን የመወያያ ጽሑፍ የመንግሥታት ግንኙነት ከፍተኛ ባለሙያ የሆኑት አቶ ኮሪ አብደላ ያቀረቡ ሲሆን የውይይቱ ተሳታፊዎች የተለያዩ ሃሳቦችን አንስተው ጥልቅ ትንታኔ ተሰጥቶባቸዋል።
ውይይቱ የሰላም ሚኒስቴር አመራሮችና ሠራተኞች የኢትዮጵያን ብሔራዊ ጥቅም ለማስጠበቅ በሚደረገው ጥረት ላይ ገንቢ ሚና ለማጠናከር የሚያስችል ግንዛቤያ እንዲያሳድጉ አስችሏል።
በውይይቱ የተነሱትን ሃሳቦች መነሻ በማድረግ የሚኒስቴሩን ቀጣይ የሥራ አቅጣጫዎች ለማጎልበት እንደሚያግዝም ተጠቁሟል።